አበበ ተሰማ ታዋቂ ኢትዮጵያዊ የባሕል ዘፈኖች ድምፃዊ ነው።
አበበ ተሰማ በ፲፱፻፳፬ ዓ.ም. በሰላሴ አውራጃ ጎሓጽዮን ከተማ አካባቢ ከሚኖር የገበሬ ቤተሰብ ተወለደ። አበበ በአደገበት አካባቢ በእርሻ እና በምንጠራ ስራ ላይ ሲሰማራ ማንጎራጎር ይወድ ነበር። በየምንጠራውም እየሄደ ያንጎራጉር ነበር። በ፲፱፻፵፪ ዓ.ም. ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በዕደ ጥበብ ማዕከል ውስጥ በሽመና ስራ ተቀጥሮ ይሠራ ነበር።
በ፲፱፻፶፫ ዓ.ም. ወደ ሙዚቃው ዓለም ለመግባት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ድምፃዊ ለመቅጠር ማስታወቂያ አውጥቶ ፈተናውን ካለፈ በኋላ በደመወዝ አለመስማማት ምክንያት ተወው። ከዚያም በአቶ ኢዮኤል ዮሐንስ አማካኝነት ሀገር ፍቅር ማህበር ተቀጥሮ ለ፫ ዓመታት ያህል ካገለገለ በኋላ ሀገር ፍቅርን ትቶ በአቶ አውላቸው ደጀኔ አማካይነት በ፲፱፻፶፯ ዓ.ም. ብሔራዊ ቴአትር ተቀጠረ።
አበበ በራሱ ግጥምና ዜማ ከ፻፹ በላይ የሚሆኑ የባሕል ዘፈኖችን በአማርኛና በኦሮምኛ ተጫውቷል። «ቢሌ ቦምቢሌ» የተባለው የኦሮምኛ ዘፈን፣ «አባይም ቢሞላ»፣ «ልወዝወዘው በእገሬ» እና «ታጠቁ ማለዳ» የተሰኙት ዘፈኖቹ በይበልጥ ለህዝብ አስተዋውቀውታል። አንጋፋው አበበ ተሰማ የኢትዮጵያ የባሕል ጨዋታ አምባሳደር በመሆን ወደ ተለያዩ የውጭ ሀገሮች በመሄድ ተሳትፏል።
This article uses material from the Wikipedia አማርኛ article አበበ ተሰማ, which is released under the Creative Commons Attribution-ShareAlike 3.0 license ("CC BY-SA 3.0"); additional terms may apply (view authors). Content is available under CC BY-SA 4.0 unless otherwise noted. Images, videos and audio are available under their respective licenses.
®Wikipedia is a registered trademark of the Wiki Foundation, Inc. Wiki አማርኛ (DUHOCTRUNGQUOC.VN) is an independent company and has no affiliation with Wiki Foundation.