ማሳጌታያውያን (ግሪክ፦ Μασσαγέται /ማሣገታይ/) በእስያ በእስኩቴስ ውስጥ በጥንት የኖረ ብሔር ነበሩ።
ሄሮዶቶስ (470 ዓክልበ. ግድም) በተለይ ስለ ማሳጌታያውያን አኗኗርና አገር መግለጫ ጻፈ (1.201-1216)። አገራቸው በአራክስስ ወንዝ ስሜንና በካስፒያን ባሕር ምሥራቅ እንደ ተገኘ መሠከረ። አራክስስ ግን ከካስፒያን ምዕራብ ስለሚገኝ፣ ከ«ያክሳርትስ ወንዝ» ወይም አሁን ሲር ዳርያ ወንዝ በላይ በአሁኑ ካዛክስታን እንደ ኖሩ ይታመናል። በግሪክና ሮማዊ ጸሓፍት ዘንድ፣ የማሣጌታያውያን ጎረቤቶች በስሜን «አስፓሲዮይ» ወይም አሽቫካ፣ በምዕራብ እስኩቴስና ዳሃይ፣ በምሥራቅ ኢሠዶናውያን (ምናልባት ከቻይና መዝገቦች የታወቀው ዉሱን ብሔር) እና በደቡብ ሶግዲያ (ኾራሳን) ነበሩ።
በአውሮፓ ከተገኙት ጌታያውያን ጋር ዝምድና እንደ ነበራቸው ይታመናል። የራባኑስ ማውሩስ 10ኛው ክፍለ ዘመን ዓም መጽሐፍ «ዴ ኡኒቬርሶ» (ስለ ዓለሙ) እንዲህ ይላል፦ «ማሣጌታያውያን በመነሻቸው ከእስኩቴስ ብሔር ናቸው፤ ማሣጌታይ የተባሉት ከባድ ወይም ብርቱ ጌታያውያን ለማለት ነው።» እንዲሁም በጥንታዊ ኢራናዊ ቋንቋዎች እንደ አቨስትኛ የ«ማሣ» ትርጉም «ብርቱ፣ ከባድ፣ ታላቅ» ነው። በተጨማሪ ከካስፒያን ባሕር ስሜን «ጢውሣጌታያውያን»፣ በጥቁር ባህርም ላይ በቱራስ አካባቢ «ቱራጌታያውያን» ተገኙ።
የፋርስ ንጉሥ ቂሮስ በ538 ዓክልበ. ከማሳጌታውያን ንግሥት ቶሚሪስ ጋር በጦርነት ሲታገል መገደሉን ሄሮዶቶስ ይለናል። ዮርዳኔስ (543 ዓ.ም.) እንደሚጨምር፣ ከዚሁ ድል በኋላ ቶሚሪስ ብዙ ሀብት በምርኮ ወስዳ ወደ አውሮጳ ባልካኖች ተዛወሩ፤ በዚያ «ቶሚስ» ከተማ (የአሁን ኮንስታንጻ፣ ሮሜኒያ) በጥቁር ባሕር ላይ ሠሩ፣ ከጎታውያን ጋራ አንድ እንደ ነበሩ ይላል።
አሚያኑስ ማርክያኑስ (370 ዓ.ም.) እንዳለው፣ ቀድሞ ማሳጌታያውያን የነበሩት ነገዶች በኋላ አላኖች ሆነው ነበር። ፕሮኮፒዮስ ደግሞ (543 ዓ.ም.) እንደሚለን ሁኖች ከነዚህ ማሳጌታውያን መጥተው ነበር።
ዮሐንስ አቨንቲኑስ (16ኛው ክፍለ ዘመን) የጻፈው፣ የጀርመን መጀመርያ ንጉሥ ቱዊስኮን የአራምን ልጆች ሞሶሕንና ጌቴርን ወደ እስኩቴስ ልኮ ልጆቻቸው ማሣጌታያውያን ከስሞቻቸው ተባሉ። ይህ ዛሬ እንደ ትክክለኛ ታሪክ አይቆጠረም።
በሌላ አስተያየት ማሣጌታያውያን የሳካዎች ክፍል ሆነው ሳካዎች ወደ ሕንድ ከወረሩ ጀምሮ በሕንድ የተገኘው ጃት ነገድ ከማሣጌታያውያን እንደ ተወለዱ ይታመናል።
This article uses material from the Wikipedia አማርኛ article ማሳጌታያውያን, which is released under the Creative Commons Attribution-ShareAlike 3.0 license ("CC BY-SA 3.0"); additional terms may apply (view authors). Content is available under CC BY-SA 4.0 unless otherwise noted. Images, videos and audio are available under their respective licenses.
®Wikipedia is a registered trademark of the Wiki Foundation, Inc. Wiki አማርኛ (DUHOCTRUNGQUOC.VN) is an independent company and has no affiliation with Wiki Foundation.