የሷሶን ግዛት በስሜን ጋሊያ (የዛሬው ፈረንሳይ አገር) የተገኘና ከሮሜ መንግሥት ውድቀት (በ468 ዓ.ም.) በኋላ ትንሽ የቆየ የሮማውያን ግዛት ነበረ።
የሷሶን መንግሥት መነሻ የሮሜ ንጉሠ ነገሥት ማዮሪያኑስ በ449 ዓ.ም. አይጊዲዩስን የጋሊያ አውራጃ ዋና አለቃ እንዲሆን በሾሙበት ወቅት ሆነ።
በ5ኛው ክፍለ ዘመን የጀርመናውያን ብሔሮች ወደ ሮሜ ግዛት እየፈለሱ ነበር፣ በተለይም ቪዚጎቶች የተባለው ትልቅ ሕዝብ ለሮሜ ሰዎች እንደ ወታደሮች ስላገለገላቸው፣ መሬት በደቡብ-ምዕራብ ጋሊያ ተሠጥተው ነበር። ብዙ ጊዜ ሳያልፍ ግን የሮማውያን ሥልጣን እየደከመ እኚህ ቪዚጎቶች በራሳቸው ንጉሥ ሥር ሆነው ግዛታቸውን ያስፋፉ ጀመር። ስለዚህ አይጊዲዩስ የተቀበለው አውራጃ በስሜን ጋሊያ ሲሆን ወደ ጣልያና ወደ ሮሜ ያገናኘው ጠባብ ስርጥ ብቻ ነበር። ይህም ስርጥ ደግሞ በማዮሪያኑስ ዘመን በጀርመናውያን ነገዶች በመያዙ፣ የአይጊዲዩስ ግዛት ያንጊዜ ከሮሜ ተቋረጠ።
ኃይለኛው ጀርመናዊ ጦር አለቃ ሪኪመር በ453 ዓ.ም. ማዮሪያኑስን ካስገደላቸው በኋላ፣ አይጊዲዩስ ሥልጣኑን በጋሊያ ጠበቀው። በ455 ዓ.ም. ከፍራንኮች ጋር ተባብሮ፣ ቪዚጎቶቹን በኦርሌያን ውጊያ ድል አደረገ። በ456 ዓ.ም. ግን አይጊዲዩስ ተገደለ፤ ልጁም ሲያግሪዩስ ግዛቱን ወረሰ። ማዕረጉ በይፋ የሮሜ አገረ ገዥ ቢሆንም፣ ጀርመናዊ ጎረቤቶቹ «የሮማውያን ንጉሥ» ይሉት ነበር። መቀመጫውም በአሁኑ ሷሶን ከተማ (በሮማይስጥ፦ ኖዊዱኑም) ነበረ። ስለዚህ በአንዳንድ ታሪክ ግዛቱ «የሷሶን መንግሥት» ወይም «የሲያግሪዩስ መንግሥት» ይባላል።
በሮሜ ጣልያ በ468 ዓ.ም. መጨረሻው ንጉሠ ነገሥት ሮሙሉስ አውግስጦስ በጀርመናዊው አለቃ ኦዶዋካር ስለ ተሻሩ፣ የሮሜ ነገሥታት ሥልጣን በምዕራብ ተቋረጠ። ሲያግሪዩስ ግን የኦዶዋካርን መንግሥት ስላልተቀበለ፣ እርሱ በስሜን ጋሊያ ገዢ ሆኖ የሮሜ ሕግጋትን አስቀጠለ።
የፍራንኮች ንጉሥ 1 ቺልደሪክ በ473 ዓ.ም. ዐርፎ፣ ተከታዩ 1 ክሎቪስ የሲያግሪዩስ ጠላት ሆነና በጦርነት አገሩን በሙሉ ያዘ። በመጨረሻ የሷሶን ውጊያ (478 ዓ.ም.) ክሎቪስ ስያግሪዩስን አሸነፈ። ከዚህ በኋላ ግዛቱ ሁሉ ወደ ፍራንኮች መንግስት ተጨመረ። ሲያግሪዩስ ወደ ቪዚጎቶች ቢሸሽም፣ ፍራንኮች ዛቻ ስለ ጣሉ ቪዚጎቶች መለሱትና ይሙት በቃ ተፈረደ።
This article uses material from the Wikipedia አማርኛ article የሷሶን ግዛት, which is released under the Creative Commons Attribution-ShareAlike 3.0 license ("CC BY-SA 3.0"); additional terms may apply (view authors). Content is available under CC BY-SA 4.0 unless otherwise noted. Images, videos and audio are available under their respective licenses.
®Wikipedia is a registered trademark of the Wiki Foundation, Inc. Wiki አማርኛ (DUHOCTRUNGQUOC.VN) is an independent company and has no affiliation with Wiki Foundation.