የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን (ፌ.ሥ.ፀ.ሙ.ኮ.) በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ውስጥ የሥነምግባር መከታተያ ኮሚሽን ነው። የኮሚሽኑ ተጠሪነት በቀጥታ ለኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ነው። የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ክቡር አቶ ዓሊ ሱለይማን ሲሆኑ ም/ኮሚሽነሩ ደግሞ ክቡር አቶ ወዶ አጦ ናቸው። ኮሚሽኑ «ሥነምግባር» (እንግሊዝኛ፦ Ethics) የተባለ በዓመት አራት ጊዜ የሚታተም መፅሄት እና «መስታወት» (እንግሊዝኛ፦ Insight) የተባለ በዓመት ሁለት ጊዜ የሚወጣ ኒውስሌተር አለው።
እ.ኤ.አ. በ1996 በብሔራዊ ደረጃ የተጀመረው የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ ፕሮግራም የሥነምግባር ንዑስ ፕሮግራምን በውስጡ የያዘ ነበር። የስነምግባር ንዑስ ፕሮግራም አንድ ፕሮጀክት ኮሚሽኑን ማቋቋም ነበር። የፕሮጀክቱም ስም የስነምግባር መከታተያና ማዕከላዊ አካል ማቋቋሚያ ፕሮጀክት የሚል ነበር። በዚህም መሰረት የፌደራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ግንቦት 16 ቀን 1993 ዓ.ም. በአዋጅ ተቋቋመ።
ኮሚሽኑ ዘጠኝ ዳይሬክቶሬቶችና ሁለት አገልግሎቶች አሉት። በተጨማሪም የኮሚሽኑን ውስጣዊ አሠራርን የሚከታተል የሥነምግባር መከታተያ ጽ/ቤት አለ። ይህም ጽህፈት ቤት በአቶ ሃረጎት አብርሃ ይመራል። የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እስከ መጋቢት ፴ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም. ድረስ 315 ሠራተኞች ያሉት ሲሆን ከዚህ ውስጥ 101 ሴቶች ናቸው።
የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ዋና መስሪያ ቤት አዲስ አበባ ይገኛል። በድሬዳዋ ከተማ የሚገኘው የኮሚሽኑ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የተመረቀው በመጋቢት ፲፩ ቀን ፳፻፪ ዓ.ም. ሲሆን በአሁኑ ወቅት 21 ሠራተኞች አሉት።
ዳይሬክቶሬት | ዳይሬክተር |
---|---|
የሀብት ማሳወቂያ እና ምዝገባ ዳይሬክቶሬት | አቶ ግርማ ወርቁ |
የሙስና ወንጀል ምርመራ እና ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት | አቶ ገብሩ ገበየሁ |
የሙስና መከላከል ዳይሬክቶሬት | አቶ አክልሉ ሙሉጌታ |
የሥነ ምግባር ትምህርት እና ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት | አቶ ብርሃኑ አሰፋ |
የሥነ ምግባር አውታሮች ማስተባበሪያ ዳይሬክቶሬት | አቶ ብርሃኑ ክፈተው |
የሰው ሀብት ሥራ አመራር | አቶ መኮንን ዘገዬ |
ዕቅድ፣ ግዥ እና ፋይናንስ ዳይሬክቶሬት | አቶ ሙላት ሸዋታጠቅ |
የጥናት እና የለውጥ ሥራ አመራር ዳይሬክቶሬት | አቶ ተስፋዬ ሻሜቦ (ተጠባባቂ) |
የኦዲት አገልግሎት ዳይሬክቶሬት | አቶ ፋኖሴ ሀሰን |
አገልግሎት | ኃላፊ |
---|---|
የህግ አገልግሎት | አቶ ብሌን ግርማይ (ተጠባባቂ) |
ጠቅላላ አገልግሎት | ጥላዬ የትዋለ |
ኮሚሽኑ ከመንግስት በ፳፻፪ ዓ.ም. 16.23 ሚሊዮን ብር፣ በ፳፻፫ ዓ.ም. 26 ሚሊዮን 93 ሺህ 930 ብር፣ በ፳፻፬ ዓ.ም. ደግሞ 34 ሚሊዮን 840 ሺህ ብር የተመደበለት ሲሆን ከሌሎች አለም አቀፍ ተቋማት በየዓመቱ የሚያገኘው ገንዘብም አለ።
This article uses material from the Wikipedia አማርኛ article የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን, which is released under the Creative Commons Attribution-ShareAlike 3.0 license ("CC BY-SA 3.0"); additional terms may apply (view authors). Content is available under CC BY-SA 4.0 unless otherwise noted. Images, videos and audio are available under their respective licenses.
®Wikipedia is a registered trademark of the Wiki Foundation, Inc. Wiki አማርኛ (DUHOCTRUNGQUOC.VN) is an independent company and has no affiliation with Wiki Foundation.